Thursday, January 11, 2018

የታላቁን ንጉሥ ልደት ለመዘከር የወርሃ ጥርን መግቢያ ለመይሳው ካሳ፤ ቋረኛው አንበሳ-የጀግንነት ልኩ፤

የታላቁን ንጉሥ ልደት ለመዘከር የወርሃ ጥርን መግቢያ ለመይሳው ካሳ፤ ቋረኛው አንበሳ-የጀግንነት ልኩ፤
ተጓዡ ጋዜጠኛ ሄኖክ ስዩም የጥር ወርን መጀመሪያ ለታላቁ ንጉሥ ለንጉሠ ነገሥት ዐፄ ቴዎድሮስ እንስጠው ብሎ ጀግናውን መተረክ ጀምሯል፡፡ ቋረኛው አንበሳ የጀግንነት ልኩ ሲል የተወለደባትን ስፍራ የማስታወሻው መጀመሪያ አድርጓታል፡፡ | ሄኖክ ስዩም በድሬ ቲዩብ
አንዷን ኢትዮጵያ ሰላሳ አርባና ሀምሳ ቦታ ቦጫጭቀው ለዕለት ደስታቸው የሚኖሩ መሳፍንት በበዙበት ዘመን አንድ ሰው ተወለደ፡፡
የዚህን ጀግና እትብት የቀረበረች ቋራ እንደምን የታደለች ናት፡፡ ቋራ ከዚያም ቀድሞ የጀግኖች ከዚያም በኋላ የጀግኖች ምድር ናት፡፡
የጥር ወርን በራፍ ታላቁን ምድር እያነሳን እንዘክረዋለን፡፡
ቋራና እንደክብሩ ከስሙ አስቀድሞ ለመጠራት የመጀመሪያው ሰው መይሳው አልነበረም፤ ለምሳሌ በጎንደር ዘመን የነበሩት የእቴጌ ምንትዋብ ልጅ ቋረኛው ኢያሱ በሚል ይጠሩ ነበር፡፡
ራሳቸው እኒያ ብርሃን ሞገሳ የተባሉት ብርቱ ሴት የጎንደር ዘመን የፖለቲካ እቴጌም ቋረኛ ናቸው፡፡ በሱሲኒዮስና በሰርጸ ድንግል ዜና መዕዋሎች የቋራን ወንድ የጦር ሜዳ ውሎ ማየት ይቻላል፡፡
ቋራ በርሃ ነው፤ ግን ደግሞ ደን የተጠቀጠቀበት፤ የዓይማ ወንዝ በረከት ያረሰረሰው፤ አባታቸው ሐይሉ ወልደጊዮርጊስ የቋራ ተወላጅ እና ስም ያላቸው ጀግና ነበሩ፡፡ እናታቸው ደግሞ የእንፍራንዟ አትጠገብ ናቸው፡፡ አትጠገብ የደንቢያ ባላባት ልጅ ናቸው፡፡
መይሳው በልጅነታቸው ፊደል የቆጠሩት ሥርዓት የተማሩት ማህበረ ስላሴ ገዳም ነው፡፡ ለዚህ ነው አረብኛ ቋንቋ እንጂ ሃይማኖት እንዳልሆነ የገባቸው፡፡
ማህበረ ሥላሴ በቋራ ምድር የሚገኝ በአብርሐ ወ አጽበሐ የተተከለ የታላላቅ ቅዱሳን አድራሻ ነው፡፡ ገዳሙ ድንበር ላይ ነው የሚገኘው፤ ድንበር ጥሶ ስለሚገባ ጠላት መይሳው ፊደል በሚማሩበት የልጅነት እድሜ የሀገር ዳር ድንበር ጉዳይንም አብረው እያጠኑ አደጉ፡፡
ዛሬ ገደባችሁ ብላ ጠዋት ማታ የምትዝተው ግብጽ የመይሳው ካሳ የልጅነት ቃታ መለማመጃ የጀግንነት ልኩን መስፈሪያ ነበረች፡፡
በወጣትነቱ የተሳተፈባቸው ውጊያዎች ግብጽ በሱዳን የኢትዮጵያን ድንበር ስትዘልቅ ሱዳን ድረስ ገብቶ አደብ ያስገዛት የነበረው ታሪክ ሺ ቦታ ተቆራርጣ የየመሳፍንቱ የአንገት ጌጥ በሆነችው ኢትዮጵያ ከዳር ዳር ናኘ፤ ይህንን ለመሰለ ጀግና ልጅን ቀድሞ መዳር የቀደመችዋ ኢትዮጵያ መሪዎች የፖለቲካ ዘዴ ነውና፤ እቴጌ መነን የልጅ ልጃቸውን ለወጣቱ ጀግና ለመዳር ልጃቸውን ራስ አሊን አሳመኑ፤ ቋራ የበጌምድር አማች ሆነ፡፡
የደሃ ደካማ የለውም የተባለው መይሳውም እንደተባለው በረታ፤ ምንትዋብን ካገባ በኋላ በዋለበት የጦር ሜዳ ሁሉ ድል ለእሱ ሆነች፡፡
ከእግዜር በታች የተባሉ መሳፍንት እያንዳንዱ ቀን እግሩ ስር የሚወድቁበት ክፍ ቀን ሆነ፡፡ ብዙ ቦታ ለብዙ እኔ ባይ መሳፍንት የሆነችዋ ሀገር ዳግም መልካም ቀን መጣላት፡፡
በጌ ምድር ከራስ ጉግሳ አንደርታ ከራስ ወልደ ጊዮርጊስ ጎን ቆም የአንድ ሀገር ልጅ ሁለት ጎራ የሚዋደቅበትን የታሪክ ቁስል የሚጠግን የብርሃን ጭላንጭል ታየ፡፡
ከጉራምባ እስከ መከሁ ለፍልሚያ የወጣው መይሳው ማታ ድሉን ማጣጣም ጀመረ፡፡
ይህ ጀግና ለኢትዮጵያ የተሰጣት ጥር ስድስት ቀን 1811 ዓ.ም. ነበር፡፡ ከአማቾቹ አንድ ሙከት የተነሳው ጀግና ኢትዮጵያን ታህል ታላቅ ሀገር እጁ ገባች፤ ጥርን ለመታሰቢያነቱ ሰጥተንዋልና ቀጥለናል፡፡

ይህን ያውቁ ኖሯል❓❓❓ አርባ አራቱ ታቦት የሚለው ታሪክ መነሻው ምንድን ነው ?

በተለምዶ ‹‹ አርባ አራቱ ታቦት›› እያልን የምንጠራቸው አብያተ ክርስቲያናት ያሉት በጐንደር ከተማ ሲሆን ስማቸውም የሚከተለው ነው፡፡
1. ፊት ሚካኤል2. ፊት አቦ
3. አደባባይ ኢየሱስ
4. ግምጃ ቤት ማርያም
5. እልፍኝ ጊዮርጊስ
6. መድኃኔዓለም7. ቅዱስ ገብርኤል
8. ጠዳ እግዚአብሔር አብ
9. አባ እንጦንዮስ10. ደብረ ብርሃን ሥላሴ
11. አደባባይ ተክለሃይማኖት
12. ሠለስቱ ምእት
13. ልደታ ለማርያም
14. አጣጣሚ ሚካኤል
15. አቡነ ኤውስጣቴዎስ
16. ቅዱስ ሩፋኤል
17. ደፈጫ ኪዳነ ምሕረት
18. ቁስቋም ደብረ ፀሐይ
19. መጥምቁ ዮሐንስ
20. በኣታ ለማርያም
21. ቅዱስ ቂርቆስ
22. ዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ
23. አባ ጃሌ ተ/ሃይማኖት
24. ፈንጠር ልደታ
25. ደብረ ምጥማቅ ማርያም
26. አባ ዐቢየ እግዚእ
27. ቅዱስ ፋሲለደስ
28. ሐዋርያት
29. ቀሃ ኢየሱስ
30. አርባዕቱ እንስሳት
31. ጎንደሮች ጊዮርጊስ
32. ጎንደሮች ማርያም
33. አበራ ጊዮርጊስ
34. ብላጅግ ቅዱስ ሚካሌል
35. አባ ሳሙኤል
36. አይራ ሚካኤል
37. ጓራ ዮሐንስ
38. ወረንግቦ ጊዮርጊስ
39. አሮጌ ልደታ
40. አዘዞ ተ/ሃይማኖት
41. ምንዝሮ ተ/ሀይማኖት
42. ሰራራ ማርያም
43. ዳሞት ጊዮርጊስ
44. ጫጭቁና ማርያም

አርባ አራቱ ታቦት የሚለው ታሪክ መነሻው ምንድን ነው ?
እውን ታቦት አርባ አራት ብቻ ?
ጎንደር በኢትዮጵያ የመንግሥት ታሪክ ከአክሱምና ላሊበላ ቀጥሎ ትልቋ የመንግሥት ማዕከል ነበረች፡፡ በመንግሥት ማዕከልነት የተቆረቆረችው በአፄ ፋሲል (1624-1660 ዓ.ም) ነው፡፡ ጎንደር የመንግሥት ማዕከል ብቻ ሳትሆን በጊዜው የመንፈሳዊ ትምህርት ማዕከልም ነበረች፡፡ በኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን የመጻሕፍት እና የአቋቋም ትምህርት ይበልጥ የተስፋፋውና በየሀገሩ ያሉ ሊቃውንት በመናገሻ ከተማዋ ጎንደር በነገሥታቱ አማካይነት በመሰባሰባቸው ሲሆን ከዚያን ዘመን ጀምሮ እስከዛሬ ድረስ መንፈሳዊ ትምህርት በስፋት የሚሰጥባት የትምህርት ማዕከል ለመሆን ችላለች፡፡
በአሁኑ ሰዓት በሰሜን ጎንደር በሚገኙ 21 ወረዳዎች ከ2117 ያላነሱ ገዳማትና አብያተ ክርስቲያናት ሲኖሩ በዋና ከተማዋ ደግሞ ከ92 ያላነሱ አብያተ ክርስቲያናት ይገኛሉ፡፡ በአብነት ት/ቤት ረገድም የመጻሕፍት ጉባዔያት፣ የአቋቋም ምስክር፣ የቅኔ አብያተ ጉባዔያት እንዲሁም የዜማ ት/ቤቶች በከተማዋ እና በዙሪያዋ በሚገኙ ወረዳዎች ይገኛሉ፡፡ በአሁኑ ሰዓት በከተማዋ ከ92 ያላነሱ አብያተ ክርስቲያናት ቢኖሩም በአብዛኛው ስማቸው ደጋግሞ የሚነሳው የ44ቱ ብቻ ነው፡፡ በተለያየ ጊዜ በተለይም ጎንደርን ከማያውቁት ሰዎች ጋር ባደረኩት ውይይት 44ቱን ታቦታተ ጎንደርን በተመለከተ የተለያየ ግንዛቤ እንዳለ ለመገንዘብ ችያለሁ፡፡ አንዳንዶቹ በመላው ኢትዮጵያ የሚገኙት የአብያተ ክርስቲያናት ታቦታት ስያሜ ብዛት ሲመስላቸው ሌሎቹ ደግሞ በጎንደር በጥምቀት በዓል ወደጥምቀተ ባህር የሚወርዱትን ብቻ ሲሉ ይደመጣሉ፡፡ ጎንደር ከተማ እየኖሩም የ44ቱን ዝርዝር በውል የማያውቁ ብዙ ሰዎች ገጥመውኛል፡፡ አርባ አራቱ ታቦታተ ጎንደር ከቤተ መንግሥቶቹ በተጨማሪ ታሪካዊዋ ጎንደር የምትታወቅበት ቅርስ ነው፡፡ ጎንደር ከተማ በአፄ ፋሲል የመንግሥት ከተማ ከመሆኗ አስቀድሞ የአካባቢው ነዋሪዎች ተክለዋቸው የነበሩ አብያተ ክርስቲያናት ነበሩ፡፡ ለምሳሌ ቀሐ ኢየሱስ፣ አርባዕቱ እንስሳ፣ አበራ ጊዮርጊስ፡፡
ጎንደር የመንግሥት ከተማ ከሆነችበት እስከ ጎንደር ዘመን ማክተሚያ ፈፃሜ መንግሥት አፄ ተክለ ጊዮርጊስ (1772-1777) ድረስ 18 ነገሥታት የነገሱ ሲሆን እነዚህም አብዛኛዎቹ አብያተ ክርስቲያናትን አሠርተዋል፡፡ እንግዲህ 44 የሚባሉት አብያተ ክርስቲያናት ጎንደር የመንግሥት ከተማ ከመሆኗ አስቀድሞ የተተከሉበትን ጨምሮ እስከ ፈፃሜ መንግሥት ተክለ ጊዮርጊስ (1772-1777) ድረስ የተተከሉትን ብቻ ሲሆን ቁጥራቸውም 44 ነው፡፡ ከዚያ ወዲህ ከዘመነ መሣፍንት እስከ አሁን የተተከሉ በርካታ አብያተ ክርስቲያናት ቢኖሩም ከ44ቱ የሚቆጠሩ አይደሉም፡፡ በአጠቃላይ አርባአራቱ ታቦታተ ጎንደር በጎንደር ዘመን በጎንደር ከተማና አካባቢው የሚገኙና የነበሩ 44 አብያተ ክርስቲያናት ጥቅል ስም ነው፡፡ ስለዚህ አርባ አራቱ ታቦት ሲባል ይህን ታሪክ ተከትሎ የመጣ ስያሜ እንጂ በቤተክርስትያናችን ቁጥር ስፍር የሌላቸው ታቦታት ነው ያሉት! ምክንያቱም ሁልጊዜም አዲስ ቤተ ክርስቲያን በሚሰራበት ጊዜ ታቦት ከእጽ ወይም ከእብነ በረድ ተቀርጾ በላዩ " ኢየሱስ ክርስቶስ አልፋ ኦሜጋ " ተብሎ ይጻፍበታል! የመጀመሪያውና የመጨረሻው ማለት ነው ፡፡ ይህ ቃል ከተጻፈበት በኋላ በኤፒስ ቆጶሱ እጅ ተባርኮና ሜሮን ተቀብቶ በመንበሩ ይሰየማል (ይቀመጣል) ፣በቅዳሴም ጊዜ ሕብስቱና ወይኑ ወደ ቤተ መቅደስ ሲገባ ቄሱ ሥርዓተ ቅዳሴውን የሚያከናውነው ሕብስቱን ሥጋ መለኮት ፣ ወይኑን ደመ መለኮት ወደ መሆን የሚለውጠው በዚህ በታቦቱ ላይ ነው ፡፡ሥጋዬን ብሉ ደሜንም ጠጡ እያለ ያመኑትን ሁሉ የሚጠራበት የምሕረት ምሥዋዕ (መሠዊ) ነው ፡፡ ታቦት በሐዲስ ኪዳን እውነተኛው የሕይወት ምግብ የክርስቶስ ሥጋና ደም የሚቀርብበትና የሚፈተትበት መሠዊያ ነው ፡፡
ስለዚህ በአርባ አራት ቁጥር ብቻ የሚወሰን ሳይሆን እልፍ አዕላፍ መሆኑን ልብ ልንል ይገባል! "ለሚጠይቃቹ ጥያቄ ሁሉ እንዴት መልስ መመለስ እንዳለባቹ ታውቁ ዘንድ ንግግራቹ ሁል ግዜ በጨው እንደተቀመመ በፀጋ ይሁን" ቆላስይስ 4:6።

የቋራው ካሳ-አንድ ሀገር የመፍጠር ህልምና የሀገር ልማት ረሃብ…

የቋራው ካሳ-አንድ ሀገር የመፍጠር ህልምና የሀገር ልማት ረሃብ፤ | ታላቁን ንጉሠ ነገሥት ዐፄ ቴዎድሮስን በጥር ወር የመጀመሪያ ሣምንት ለመዘከር ስለ ታላቁ ንጉሥ ትረካውን ቀጥሏል፡፡ አንድ ሀገር የመፍጠር ህልም በሀገር ልማት ርሃብ ላይ ሲል የታላቁን ንጉሥ ገድል ይተርክልናል፡፡ | ሄኖክ ስዩም |
ሁለት ነገር በአንዴ አርግዞ በየቁራጭ ርስቱ እፎይ ካለው መሣፍንት የቀደመ ህልም አለመ፡፡ አንድም ብዙ ሀገር አንድ ስለማድረግ፤ የምን ብዙ ሀገር ብሎ ከታሪክ የሚቃረን ብዙ ሰው ይኖራል፡፡
እውነቱን ግን አንደብቀውም፤ የጠገበ መስፍን ሁሉ ሰፈሩን ሀገር እያለ አንዷን ታላቅ ሀገር ሺ ቦታ በትነዋት የዋሁን ገበሬ ለየቀዬው ጦር ይሰለፍ ዘንድ አበሳውን አሳዩት፡፡ ደግሞም አንድ ሀገር የመመስረቱ ጉዞ የገዛ ቤተሰብ ከንቱ ምኞት ከማፍረስ ጀመረ፡፡
ከአራት መከራክር እስከ በጌምድር፣ ከጃናሞራ እስከ የጁ የነበረው የየራስ ህልም አንድ ህልም ሆነ፡፡ ወዲህ ደግሞ ሌላ ምኞት አለ፡፡ ዘምና የለማች ሀገር መፍጠር፤ ቱርክ በመሳሪያው የማያስፈራራት፤ ግብጥ በጥበቡ እንቅልፍ የማይነሳት፤ አውሮጳ በመላው የማያንበረክካት ሀገር መፍጠር፡፡ መይሳው የወንዜ ሰው አልነበረም፡፡ ስለ ወንዙ ሳይሆን ስለ ሀገሩ የሚጨነቅ መሪ ሆነ፡፡
የተበደሉት ከበቡት፤ የበደሉት ተዋጉት፡፡ ድል ለጭቁኖች እየሄነች የመጨረሻው ጦር ቧሂት ላይ ተፈታ፡፡ ዘር የሚቆጥረው መንፈስ በብርቱ ክንድ ተረታና ደረስጌ ዘውዱን ደፋ፡፡
መይሳው ወንዜ አምላኪ ቢሆን መናገሻው ገለጉ በሆነች፤ ግን መጣ፡፡ ጋፋት መሀል ጥበብን ፍለጋ፤ ደግሞም ወረደ መቅደላ ታላቁን የምኞቱን አምባ ሊገነባ፡፡
Henry Stern taken prisoner by Tewodros II in Abyssinia in 1863 Rev Henry Aaron Stern, 1820 to 1885, British missionary Tewodros II, baptized Theodore II c 1818 to 1868 Emperor of Ethiopia From El Mundo en la Mano published 1875

ራስን ማጥፋት ምን ጀግንነት ነው ቢል የዛሬ ሰው አይገርመኝም፤ ዘመን በቆሙበት የሚመተር እውነት አለው፡፡ ስንቱን ዝም ያሰኘው ጀግና ራሱን ሲያጠፋ ፈሪ ተባለ፡፡ በሞት ስርየት እንዳለ ከነበር እንማራለን፡፡
አቤት ያቺ ገጣሚ “የሸዋንም ንጉሥ ሲንቁ ሲንቁ የትግሬንም ንጉሥ ሲንቁ ሲንቁ……” ወንድ አለራስዎ ገለውም አያውቁ አለች፡፡
ታሪክ የጀግንነትን ልክ በሞቱ ለምን ለካው? እንደተወለደ ራሱን ያጠፋ ሰው እኮ አልነበረም፡፡ አይሻል ላይ ድል አጣጥሟል፤ ማን ነክቶኝ ባዩን ራስ አሊን እያሳደደ፡፡
ጉራምባስ የማን ክንድ ታይቶ፤ ግብጥን ከአይማ ወንዝ እስከ ካርቱም ማን አሳደዳት? ደጃች ውቤን ማን ማረከ? በጦር ሜዳ ውሎ ማሸነፍን ለማያውቅ ራስ መግደል ፍርሐት ይሆናል፡፡
ሁሉን አሸንፎ ራስን ስለ ሀገር ክብር አሳልፎ መስጠት ግን የጥቂቶች ናት፡፡ ጥር ነው፡፡ እኒህ ታላቅ ንጉሥ የተወለዱበት ወር፡፡ ገና የምንትዋብ ፍቅር የጀግነነት መንገድ ሲሆን እናያለን፡፡ የጎንደሩን የቁንጅና ውድድር እናነሳለን፡፡ ህልምህን አሳየን ብለን ምኞቱን እመኛለን፡፡ ይቀጥላል…