Wednesday, August 2, 2017

​ቅዱስ ጊዮርጊስ ታደለ መንገሻን ሲያስፈርም አሜ መሐመድን ለማስፈረም ተስማምቷል

የፕሪምየር ሊጉ ቻምፒዮን ቅዱስ ጊዮርጊስ ደደቢትን ለመቀላቀል ተስማምቶ የነበረው ታደለ መንገሻን ባልተጠበቀ ሁኔታ ሲያስፈርም አሜ መሐመድን ለማስፈረም ተስማምቷል፡፡













ያለፉትን ሁለት የውድድር አመታት በአርባምንጭ ያሳለፈው ታደለ መንገሻ ወደ ቀድሞ ክለቡ ደደቢት ለመመለስ ተስማምቶ የነበረ ቢሆንም ባልታወቀ ምክንያት ሳይፈርም ቀርቶ በ2000 እና 2001 የውድድር አመታት ወደተጫወተበት ቅዱስ ጊዮርጊስ ተመልሶ የ2 አመታት ኮንትራት መፈራረሙን የቅዱስ ጊዮርጊስ ይፋዊ የፌስቡክ ገፅ አስታውቋል፡፡

ሌላው ለቅዱስ ጊዮርጊስ ፊርማውን ያኖራል ተብሎ የሚጠበቀው አሜ መሐመድ ነው፡፡ አሜ ከጅማ አባ ቡና ጋር የ1 አመት ውል የነበረው በመሆኑ ተጫዋቹ ለጅማ አባ ቡና የውል ማፍረሻ 1,000,000 ብር ለመክፈል ተስማምቶ መልቀቂያ ተቀብሏል፡፡ በቀጣዮቹ ጊዜያትም በይፋ ለክለቡ የሚፈርም ይሆናል፡፡

መቐለ ከተማ ሁለት አዳዲስ ተጫዋቾች አስፈረመ

አዲሱ የፕሪምየር ሊግ ክለብ መቐለ ከተማ ጫላ ድሪባ እና ታደለ ባይሳን የግሉ አድርጓል፡፡












ጫላ ድሪባ አዳማ ከተማን ለቆ የተጠናቀቀውን የውድድር አመት በወልድያ ያሳለፈ ሲሆን ከበድሩ ኑርሁሴን ጋር በመፈራረቅ በወልዲያ አጥቂ መስመር ላይ ከአንዷለም ንጉሴ ጋር ሲሰለፍ ቆይቶ ኮንትራቱን በማጠናቀቁ ወደ መቐለ ተጉዟል ፡፡

ሌላው ለክለቡ የፈረመው ታደለ ባይሳ ነው፡፡ ከፋሲል ከተማ ጋር ወደ ፕሪምየር ሊጉ አብሮ ያደገው የመሀል ተከላካዩ ታደለ ዘንድሮ የሊጉ ክስተት በነበረው ፋሲል ከተማ በስፍራው ከከድር ኸይረዲን ጋር በመፈራረቅ የተጫወተ ሲሆን በተሰለፈባቸው ጨዋታዎች ቡድኑን በአምበልነት ሲመራ እንደነበር ይታወሳል፡፡
መቐለ ከተማ ወደ ፕሪምየር ሊጉ ማደጉን ካረጋገጠ ወዲህ በተጫዋቾች ዝውውር ላይ ተሳትፎን እያደረገ የሚገኝ ሲሆን የሁለቱን ተጫዋቾች ጨምሮ እስካሁን ያስፈረማቸው ተጫዋቾች ቁጥር 5 ደርሷል፡:

ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ 6 ተጫዋቾችን አስፈረመ

ለመጀመርያ ጊዜ ወደ ፕሪምየር ሊጉ ያደገው ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በዛሬው እለት የ5 አዳዲስ ተጫዋቾችን ፊርማ ሲያጠናቅቅ አንድ ተጫዋች በቋሚነት አስፈርሟል፡፡ እንየው ካሳሁንንም ለማስፈረም ተቃርቧል፡፡


ያለፉትን ሁለት አመታት በኢትዮ ኤሌክትሪክ ያሳለፈው ዋለልኝ ገብሬ ወደ ወልዋሎ ማምራቱ የተረጋገጠ ተጫዋች ነው፡፡ የመሀል አማካዩ በኤሌክትሪክ የአማካይ ክፍል ላይ ከበኃይሉ ተሻገር ጋር በመፈራረቅ አመዛኞቹ ጨዋታዎች ላይ መሰለፍ ችሏል፡፡

ቢንያም አየለ ሌላው የክለቡ ፈራሚ ነው፡፡ አዳማ ከተማ በ2007 ወደ ፕሪምየር ሊግ በተመለሰበት አመት 3ኛ ሆኖ እንዲያጠናቅቅ ከተጠባባቂ ወንበር እየተነሳ ባስቆጠራቸው ወሳኝ ጎሎች የረዳ ቢሆንም ቀጥሎ ባሉት አመታት ግን ጥቂት ጨዋታዎች ላይ ብቻ ተሰልፎ ተጫውቷል፡፡

ተስፋዬ ዲባባ ወደ ወልዋሎ ያመራ ሌላው ተጫዋች ነው፡፡ የቀድሞው የሙገር ሲሚንቶ ፣ ኢትዮጵያ ቡና እና ንግድ ባንክ የመሀል ተከላካይ በድሬዳዋ ከተማ ያለፉትን ሁለት አመታት ያሳለፈ ሲሆን በቋሚነትም ቡድኑን አገልግሏል፡፡



ክለቡ ከፕሪምየር ሊጉ በተጨማሪ ሁለት ተጫዋቾችን ከከፍተኛ ሊጉ አስፈርሟል፡፡ ግብ ጠባቂው ዘውዱ መስፍን የባህርዳር ከተማ ውሉን አጠናቆ ወደ ወልዋሎ አምርቷል፡፡ ከዚል ቀደም በቅዱስ ጊዮርጊስ ፣ መተሀራ ስኳር እና ኢትዮጵያ ክለቦች በፕሪምየር ሊጉ የተጫወተው ዘውዱ ወደ ሊጉ ዳግም ተመልሷል፡፡ እዮብ ወልደማርያምም የወልዋሎ ንብረት የሆነ ተጫዋች ነው፡፡ እዮብ ወልዲያ ወደ ፕሪምየር ሊጉ እንዲገባ ቁልፉን ሚና ከተጫወተ በኋላ ክለቡን ለቆ አመቱን በአማራ ውሀ ስራ አሳልፏል፡፡

ወልዋሎ ካስፈረማቸው አዳዲስ ተጫዋቾች በተጨማሪ አሳሪ አልመሀዲን በቋሚነት አስፈርሟል፡፡ አሳሪ በውድድር አመቱ አጋማሽ ከድሬዳዋ ከተማ በውሰት አምርቶ መልካም ግልጋሎት ማበርከቱን ተከትሎ በቋሚነት ክለቡን ተቀላቅሏል፡፡

እንየው ካሳሁን ለክለቡ ለመፈረም ከስምምነት የደረሰ ተጫዋች ነው፡፡ የቀኝ መስመር ተከላካዩ በአዲስ አበባ ከተማ ያለውን የአንድ አመት ውል ማፍረስ የሚጠበቅበት ሲሆን ውሉን በስምምነት አፍርሶ መልቀቂያውን ሲቀበል ለወልዋሎ በይፋ ይፈርማል ተብሏል፡፡

ወልዋሎ ከቀናት በፊተ የግ መስመር ተከላካዩ ሮቤል ግርማን በሁለት አመት ኮንትራት ማስፈረሙ የሚታወስ ሲሆን የበረከት አማረ ፣ ሳምሶን ተካ እና ኤፍሬም ጌታቸውን ውል ማደሱ ታውቀል፡፡